በደብረ ኤልያስ በሚገኙ አራቱ ገዳማት ውስጥ አንድ መነኩሴ ብቻ በሕይወት መገኘታቸውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስታወቀች።
በአማራ ክልል ምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ ሥር ባሉ አራት ገዳማት ከግንቦት 18 እስከ 23/2015 ለተከታታይ አምስት ቀናት “የታጠቁ ኃይሎች በገዳሙ ውስጥ ይገኛሉ” በሚል ዘመቻ መደረጉንም ቤተክርስቲያኗ ገልጻለች።
በዚህ ዘመቻም እስካሁን ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ በርካታ መነኮሳት መሞታቸውን፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የገዳማት አሥተዳደር መምሪያ ኃላፊ መጋቤ ካህናት አባ ሀብተጊዎርጊስ አሥራት የተናገሩት ለአዲስ ማለዳ ነው።
በአራቱም ገዳማት አቢያተ ክርስቲያናት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱንም ሃላፊው ተናግረዋል፡፡
በዚህም በገዳሙ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች “ሕግ ማስከበር” ያሉትን ዘመቻ ከማካሄዳቸው በፊት በርካታ መነኮሳት እና አገልጋዮች ይኖሩ እንደነበር ገልጸው፣ የገዳማት አስተዳደር መምሪያው ወደ ሥፍራው ባቀናበት ወቅት የተገኙት አንድ መነኩሴ ብቻ መሆናቸውን በግልጽ አስቀምጠዋል።
“መሞታቸው ከታወቀው መነኮሳቱና አገልጋዮች ውጭ ሌሎቹ የት እንደገቡ አይታወቅም፡፡” ያሉት ኃላፊው፤ በገዳሙ ውስጥ ባለው ሰፊ የአትክልት እርሻ በርካታ ያልተቀበሩ አስከሬኖች መኖራቸውንና በአካባቢው ከፍተኛ የአስከሬን ሽታ መኖሩንም ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡
የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች “በገዳሙ የታጠቁ ኃይሎች መሽገዋል” በሚል ኦፕሬሽን ቢያደርጉም፤ በተለያዩ ጊዜያት ሽፍታዎች የገዳሙን ንብረት ለመዝረፍ ወደ ሥፍራው ይመጡ ስለነበር፣ መነኮሳቱ ምሽግ ቆፍረው ንብረቱን ከዝርፊያ ለማዳን እና ሕይወታቸውንም ለመታደግ ጥረት ሲያደርጉ እንደነበርም አመልክተዋል።
በተደረገው ዘመቻም የሥላሴ፣ የኪዳነምሕረት፣ የኤልያስ እና የጊዮርጊስ አቢያተ ክርስቲያናት ጉዳት እንደደረሰባቸውም ገልጸዋል።
አቢያተ ክርስቲያናቱ የውጭ ክፍላቸውን ጨምሮ ቅኔ ማሕሌቱ፣ ቅድስቱ እና ቤተመቅደሱ ላይ የደረሰው ድብደባ እጅግ ከፍተኛ መሆኑንም አስረድተዋል።
“በተለይ በኪዳነምሕረት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ላይ የደረሰው ጉዳት ከኹሉም የከፋ ነው፡፡” በሚል ገልጸውታል።
ንዋያተ ቅድሳትን ጨምሮ የቤተ መቅደስ መገልገያዎች መውደማቸውን እና ጉልላቱም ተመትቶ መውደቁን ሃላፊው ተናግረዋል።