(ኢትዮ 360 - ግንቦት 24/2015)በአዲስ አበባ የነዋሪው የኋትስ አፕ ገጽ እየተበረበረ ነው።
- Ethio 360 Media 2
- Jun 1, 2023
- 1 min read
በአዲስ አበባ ከተማ በኦህዴዱ ቡድን የሚታፈኑስ ሰዎች ሁሉ በአሸባሪነት ከተፈረጁ ሰዎች ጋር ግንኙነት አላችሁ በሚል ስልካቸው እየተነጠቀ እነሱም ወደ ማጎሪያ እየተወሰዱ መሆኑን የኢትዮ 360 ምንጮች ገለጹ።
በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች በድንገት የሚካሄዱ ፍተሻዎች መኖራቸውን ተናግረዋል።
ፍተሻው ደግሞ የሚጀምረው የእጅ ስልክህን አምጣ በሚል መሆኑንም ሳይጠቁሙ አላለፉም።
ስልኩን ከነጠቁ በኋላም በቀጥታ የሚሄዱት ወደ ግለሰቡ የኋትስ አፕ ገጽ መሆኑንም ሳይጠቁሙ አላለፉም።
በዚህ ፍተሻ ውስጥ በአሸባሪነት ከተፈረጁት ሰዎች ጋር በስም እንኳን የሚመሳሰል ከተገኘ የስልኩ ባለቤት በቀጥታ ወደ ማጎሪያው ይወሰዳል ሲሉ የኢትዮ 360 ምንጮች ገልጸዋል።
በየክፍለከተማው፣በየትምህርት ቤቱ፣በየመንግስት መስሪያ ቤቱና በየቦታው ኢትዮ 360ን ታዳምጣላችሁ፣መረጃ ትሰጣላችሁ በሚል በርካታ ንጹሃን ዜጎች እየታፈኑና እየተንገላቱ መሆኑን ኢትዮ 360 በመረጃው ማውጣቱ ይታወሳል።
የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ሳይቀር ወላጆቻችሁ የትኛውን ጣቢያ ነው የሚከታተሉት በሚል ህጻናቱን እያዋከበ መሆኑንም ኢትዮ 360 በሰሞኑ ካወጣቸው መረጃዎች መካከል አንዱ ነበር።